19/04/2026
🥘 የተገፋ እንጀራ
ከእናቴ ጋር በጠዋቱ ያጣላን "ቀይ ወጥ" ነበር። "ቀይ ወጥ አልወድም!" እላታለሁ፤ እሷ ግን እንኳን ሌላ ልትሰራልኝ ቀርቶ ቁጣዋን አወረደችብኝ። እኔም በብስጭት እየተመናቀርኩ ከቤት ልወጣ ስል "ልጄ አንዴ ና..." አለችኝ። ድምኵ ወዲያው ሰከን ብሏል። 😠💨
እኔም "ድሮም የእናት አንጀት!" ብዬ በልቤ እያሰብኩ ወደ ኋላዬ ተመለስኩ። ለወጉ ነው እንጂ ሆዴም ተርቧል። "አቤት እቴት... ሌላ ወጥ አለ እንዴ?" አልኳት በጉጉት። 🍲
እሷ ግን እንዲህ አለችኝ፦ "ሌላ ወጥ የለም! ግን ይቺን እንጀራ ይዘህ በር ላይ ለ10 ደቂቃ ብቻ ከቆምክ፣ የምትወደውን ምግብ እሰራላችኋለሁ።" አልደበረኝም፤ ሳህኑን ተቀብያት ወደ ውጭ ወጣሁ። በልቤ ግን "በር ላይ ደፍቼው እመለሳለሁ" ብዬ እያሴርኩ ነበር። እቴትም ወደ ጓዳዋ ገባች። 🚶♂️🍽️
ሰሀኑን ይዤ እንደወጣሁ ብዙም አልቆየሁም፤ ከፊቴ አንዲት ምስኪን ሴት ልጇን እየጎተተች መጣች። ቆማ ቁልጭ ቁልጭ እያለች ታየኝ ጀመር። አይኗ እንባ አቆሯል፤ ልጇም የቀሚሷን ጫፍ ይዛ አይኗን ከሳህኑ ላይ አልነቀለችም። ልመና መሆኑ ገብቶኝ "እንኪ ብዪ" ብዬ እጄን ዘረጋሁላት። 👩👧🥺
ሴትየዋ ግን ባለማመን ስሜት እያየችኝ አልተቀበለችኝም። "እውነትህን ነው? ለኔ ነው? ማለቴ... ንፁህ እንጀራ እኮ ማንም ሰጥቶን አያውቅም። በዛ ላይ ደግሞ የስጋ ወጥ!" አለች። ልትቀበለኝ ስትል ደግሞ በፍርሃት ወደ ኋላ ትላለች። ያወራችው ቃል ሰውነቴን ውርር አደረገኝ። 💔
"ያዢው... የናንተ ነው፤ በዓል እኮ ነው" አልኳት። 🤲
እሷ ግን ትንፋሿን እያቃሰተች "አይ... በዓል እኮ ሦስተኛ ቀኑ ነው። ሰው ስጋ በልቶ ከሰጠን ትራፊ ውስጥ ያልተጋጠ አጥንት እንኳ አላገኘንም። ወንድሜ አመሰግናለሁ! ንፁህ እንጀራ እንደሰጠኸን፣ አምላክ ንፁህ ሕይወት ይስጥህ!" ብላ ምርቃቷን አዥጎደጎደችው። 🙌✨
እኔም "አሜን! አሜን!" እያልኩ ወደ ቤት ስመለስ እቴት በር ላይ ቆማ ትጠብቀኝ ነበር። "እንጀራውስ?" አለችኝ። 🧐
"አንዲት ምስኪን ሴት ወሰደችው። ንፁህ እንጀራ ከበላሁ ቆየሁ ብላ በጣም ተደሰተች" አልኳት። የፀፀት ስሜት እየተሰማኝ እንደሆነ እቴትም አስተውላለች። እናቴም በቀስታ ጠየቀችኝ፦ "እና... አሁን ሌላ ምግብ ልስራልህ?"
"ኧረ በፍጹም! ያለውን እበላለሁ" አልኳት። 🍽️
እቴትም በጥልቅ ትምህርት እንዲህ ስትል መከረችኝ፦
"ልጄ አየህ? እኛ የገፋነው እንጀራ ለአንዳንዱ ብርቁ ነው። ስንቱ በተገፋ እንጀራ ሕይወቱን እንደሚመራ ታውቃለህ? አንተ 'በቃኝ' ብለህ በደፋኸው ስንቱ ረሃቡን ያስታግሳል? አንተ 'ንፁህ እንጀራ አልበላም' ብለህ ስትወጣ፣ የተገፋ እንጀራ ፍለጋ ከቤቱ የሚወጣ ምስኪን ሞልቷል። በሕይወትህም እምቢ ብለህ የገፋሃቸው እድሎች ለሌላው መሰጠታቸው ስለማይቀር፣ እንጀራህን ከመግፋትህ በፊት ትንሽ አስብ። ላንተ የረከሰው ለሌላው የከበረ ሊሆን ይችላል!" 👵❤️🙏